Thursday, January 29, 2026
ጥር 21 ቀን የእመቤታችን በዓለ ዕረፍት
Monday, January 26, 2026
ባህልና ሃይማኖት
ሃይመነ አሳመነ ፤ ካለው የግዕዝ ግሥ የተገኘ ሲሆን “ማመን፣ መታመን፣ እምነት፣ ጽኑ ተስፋ፣ በልብ በረቂቅ ሐሳብ የሚሣል ማለት ነው፡፡ ትርጉሙም በአንድ አምላክ ማመን እና ለአንድ አምላክ መታመን ማለትን ያመለክታል ፤ በዓይናችን ለምናየው ለግዙፉ ዓለምና ለማይታየው ለረቂቁ ዓለም ፈጣሪ አስገኝ ፣ መጋቢ አለው ፤ እሱም እግዚአብሔር ነው ብሎ ማመን ማለት ነው ።(አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መዝገበ ቃላት፣ ገጽ ፫፻፷፱) ይህ የሁሉ ፈጣሪ ደግሞ እግዚአብሔር ነው! ታዲያ ሁሉን ያስገኘ (የፈጠረ) እግዚአብሔር መሆኑን ያወቅነው በሃይማኖት ነው፤ በእምነት ነው፤ በኋላም “መንግሥተ ሰማያትን ያወርሰናል” ብለን ጽኑ ተስፋ እናደርጋለን፡። ሃይማኖት የሚፈጸም፣ የሚሆን፣ በዓይን የማይታይ፣ በሥራ የሚገለጥ ረቂቅ የሆነ ነው፡፡
ሃይማኖት ከእግዚአብሔር ጋር የምንገናኝበት ረቂቅ የሆነ (በዓይን የማይታይ) መንገድ ነው፤ መንገድ ሩቅ እና ሩቅ ያሉትን ሰዎች እንደሚያገኛኝ ሃይማኖትም የፍጥረታት ፈጣሪ እግዚአብሔርን እና እኛን ሰዎችን ስለምታገናኘን በመንገድ ተመሰለች፡፡
ስለ ሃይማኖት በጥቂቱ ገለጽን እንጂ ሃይማኖት ብዙ ምሥጢር እና ትርጉም ያላት ናት! እምነትን (ሃይማኖትን) ከምግባር ጋር ማጣጣም ያስፈልጋል፤ እምነትና ሥነ ምግባር አብረው ሲሆኑ ነው እምነታችን ጽኑ ሆኖ ኃይልና ብርታት የሚሆነን፤ ስለዚህ ሃይማኖታችንን በሥራ ሊገለጥ ያስፈልጋል፡፡
ቅዱስ ጳውሎስ ለኤፌሶን ክርስቲያኖች በላከው መልእክቱ ‹‹..ፍሬ ከሌለው ከጨለማ ሥራ ጋር አትተባበሩ…›› በማለት እንደ መከራቸው እምነታችን በሥራ የተገለጠ ፍሬን የሚያፈራ፣ ጨለማ ከተባለ ክፉ ምግባር መለየት እንዳለበት አስተምሮናል፡፡ (ኤፌ.፭፥፲፩)
እንዲሁም ባሕል ማለት የአንድ ኅብረተሰብ አኗኗር ነው። እንደ የሰው ልጅ ጥናት «ባህል» የኅብረተሠቡ ቋንቋ ፣ ሥነ ጥበብ ፣ ሥነ ጽሑፍ ፣ ሙዚቃ ፣ ጭፈራ ፣ ቴክኖሎጂ ፣ አበሳሰል ፣ አለባበስ፣ ስነ ሕንጻ ፣ ሕግ ፣ አስተያየት፣ ፍልስፍና ፣ አፈ ታሪክ እና ብዙ ሌሎች ረገዶች ያጠቅልላል።



