ቅዱሱ መጽሐፋችን መጽሐፍ ቅዱስ ወንድም ወንድሙን መግደል የጀመረበትን ምክንያት በግልጽ ይነግረናል ዘፍ 4፥8 ነገር ግን ምክንያቱን ለመቀበል ከአእምሮ በላይ በመሆኑ እጅግ ያስደንቃል። እንኳን ሰው ይቅርና እንስሳ የራሱን ወገን በበጎ የሚያይበት ተፈጥሯዊ ስጦታ ታድሏል፦ ነገር ግን የሰው ልጅ ከእንስሳት አንሶ ሰው ሰውን እየበላ የክፋት እርሃቡን ለማስታገስ ሲሮጥ ማየት እጅግ ያሳዝናል። ሰላማውያን የምንባለውም እኛ ከመደጋገሙ የተነሳ እየለመድነው በመምጣታችን እንደቁም ነገር ለመቁጠር እየተቸገርን እንደሆነ በግልጽ እየታየ ነው። ሰሞኑን በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ አርሲ ዞን በተለያዩ ወረዳዎች ሥር የሚገኙ በርካታ ምዕመናን በጽንፈኞች እንደተገደሉ ሰምተናል። ይሁን እንጅ ከመንግሥትም ሆነ ከቤተክህነት ለሟቾችም ሆነ ለቤተሰቦች እንደዜጋ እና እንደ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ምዕመን ክብር እንዳልተሰጣቸው በተላለፉት መልእክቶች መረዳት ይቻላል። የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ምዕመን መገደሉ በዚህ ደረጃ መቅለሉ በጣም ያሳዝናል።
የንፁሐን ደም የሚያመጣውን ወይም ያመጣውን መዘዝ ማወቅና መረዳት ለመንግሥትና ለሃይማኖት መሪዎች እንዴት ተሳናቸው? እንዲሁም ይህን በየጊዜው የሚፈስ ደምና እንባ የምንመለከት ወገኖች እንዴት በጋራ መጮህ አቃተን? ብለው የሚጠይቁ ብዙዎች ናቸው። ህጻናት፣ እናቶች፣ አባቶች፣ ዲያቆናት፣ ካህናት፣መነኮሳት (እስከ አሁን ጳጳሳትን አይጨምርም ለወደፊቱ ግን ስጋት አለን) ናቸው ደማቸው እየፈሰሰ ያለው። ማነው የንጹሐንን ደም ከመፍሰስ መታደግ ያለበት? የመንግስትም ሆነ የሃይማኖት መሪዎች ዘመኑን የዋጀ የአመራር ሥርዓት መዘርጋት ካልቻላችሁ ኃላፊነታችሁን እየተወጣችሁ አይደለም። ህዝብ መሪ አለኝ ብሎ ከልፋቱ ጥሪቱን ግብር እየከፈለ የሚኖረው ሰላምና ደህንቱን የሚያስጠብቅለት አካል አለኝ ብሎ አምኖ ነው።
