Wednesday, May 30, 2018

ከቀድሞው ይልቅ ያሁኑ ይደንቃል።


የሰው ሃሳብና የእግዚአብሔር መንገድ የተራራቁ በመሆናቸው ብዙ ጊዜ የምንጠብቀው ሳይሆን ያልተገመተው ሲሆን ማየት የተለመደ ነው። እግዚአብሔር ሁሉን አድራጊ በመሆኑ የሚሳነው የለም ነገር ግን ሁሉን የሚያደርግበት ጊዜ አለው። ዛሬ ላይ ሆኘ ምነው አሁን እያየንና እየሰማን ያለነው ነገር ከጥቂት ዓመታት በፊት ሆኖ ቢሆን ለማለት አሰብኩና የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራ አለማስተዋል ነው ብየ እራሴን ወቀስኩ። ያለፈው ኃዘን ባይኖር የዛሬው ደስታ የለም። ትላንት መስዋእት የሆኑ ሰዎች ባይኖሩ የዛሬው ሰላም ትልቅ ቦታ አይሰጠውም ነበር። ሁልጊዜም አንዱ እየቀለጠ ለብዙዎች ማብራቱ የተለመደ ነው። ለለወደፊቱ አንዱ እየሞተ ሌላው የሚኖርባት ሀገር እንዳትኖረን በጋራ ማሰብ አለብን።

ካለፉት ጥቂት ወራት ወዲህ የሰላም መልእክት በሀገራችን እየጎረፈ ነው።  ይህ የሰላም መልእክት የናፈቀው ህዝብ ሰላምን መስበክ ከናፈቀው መሪ ጋር ሲገናኝ ሰኔና ሰኞ ሆነ ማለት ይህ አይደል? አሁን እየታየ ያለውን የሰላም መንፈስ በቁመተ ሥጋ ሆነው ሳያዩ ላለፉ ወገኖች እጅግ እናዝናለን። የሰላም መንገድ ተሰውራ ብዙዎች አጥፊ ብዙዎች ተጎጅ ሆነው አልፈዋል። ማለፍ የማይቀር ቢሆንም ሰላምን አጥቶ ማለፍ ለየትኛውም ወገን ቢሆን አሳዛኝ ነው። ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት" "፤ ከክፉ ሽሽ መልካምንም አድርግ፤ ሰላምን እሻ ተከተላትም። " (መዝ 34: 14) እንዳለው ሰላምን ከሁሉ አስቀድሞ መፈለግ ይገባል። አሁንም ለኛ የሚሆን ብዙ ሰላም አለ። ብዙ በረከት የሚገኝበት ሰላም በፍቅርና በመተሳሰብ የሚመጣ በመሆኑ ያለፈውን ክፉ ሃሳብ አስወግደን ወደ ፍቅር እንምጣ። ባለፈው ብዙዎችን አጥተናል ከዚያም አልፎ የሀገሪቱ ህልውና አደጋ ላይ ስለነበር ብዙ ተጨንቀን ነበር። ካጣነው ሁሉ በላይ የሀገር መኖር ከሁሉ ይበልጣልና እግዚአብሔር ይመስገን። ከሰላም እርቀን በነበርንበት ዘመን ያጣነውን ነገር በገንዘብ መተመን አይቻልም። የሰው ህይዎት በገንዘብ አይተመንምና። 

Saturday, May 19, 2018

የጥፋት ርኵሰት በማይገባው ስፍራ ቆሞ ብታዩ፥ አንባቢው ያስተውል ማር 13፥14


አባቶቻችን በአድዋ የፈጸሙትን ጀግንነት እያወሳን የደም ዋጋ የተከፈለበትን ማንነት እየጣልን የምንሄድ ከሆነ አደራ በላ ትውልድ ተብለን በታሪክ እንመዘገባለን። የኛ ትውልድ ይህን ድንበር መጠበቅ ካልቻለ ያለፉት አባቶቻችን በመንፈስ የሚመጣው በግልጽ በመመስከር እንደሚያዝኑብን ለማመን ከባድ አይሆንም። በኛ ዘመን የተበላሸውን ታሪክ የሚወዳደር ዘመን አለብሎ መናገር ዋሾ ያሰኛል። ኢትዮጵያ የሚጠበቅ ታሪክ ያላት ሀገር እንጅ አዲስ ታሪክ የሚሰራላት አይደለችም። የነበራትን ክብር ማስጠበቅ ባለፈው ከተሰራው የጀግንነት ታሪክ ያላነሰ ክብር የሚያሰጥ ተግባር ነው። ይሁን እንጅ የአሁኑ ትውልድ የሚማርክ ሳይኖር በፈቃዱ እጁን እየሰጠ ይመስላል። የሰሞኑ መወያያ ርእስ የሆነው ጉዳይ ጆሮን ጭው የሚያደርግ፣ ኢትዮጵያን ከክብሯ የሚያዋርድ ለብዙዎች መርዶ የሆነ ዜና እየሰማን ነው። የሀገር እድገት፣ የዘመን ስልጣኔ  ሀገራችን ገብቶ ከድህነት ተላቀን በርኃብና በበሽታ የሚያልቀው ወገናችን እግዚአብሔርን አመስግኖ የሚቀምሰው ምግብ ያገኛል ስንል በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንዲሉ ሰዶምና ገሞራን በእሳት እንዲጠፉ ምክንያት የሆነው የኃጢአት ርኩሰት ያለምንም ከልካይ አዲስ አበባን እያዳረሳት እንደሆነ እየተሰማ ነው። ችግራችን ዘርፈ ብዙ እንዲሆን ብዙ የሰሩ አካላት ያሰቡት ሁሉ እንደተሳካላቸው እየሆነብን ያለው ነገር በቂ ማሳያ ነው።



Monday, May 14, 2018

የዶ/ር ዓቢይና የስርዓቱ ፍጥጫ

የተስተካከለ መንገድ ካለ በአግባቡ መጓዝ ይቻላል። ወጣ ገባና ኮረኮንች የበዛበት መንገድ እንደ ልብ ሊያራምድ አይችልም። ሥርዓት ሰዎችን ካልጠቀመ ችግር አለበት ማለት ነው። ሥርዓት ያስፈለገው የሰው ልጆችን እኩልነት ለማስፈን መሆኑ የታወቀ ነው። ይህም ሆኖ ሥርዓት አስከባሪ እስካልተገኘ ድረስ ፋይዳ የለውም። ሥርዓት ካለ የሚበደል ሰው መኖር የለበትም። በየስፍራው ሰዎች የመኖር ህልውናቸው የሚገፈፍ ከሆነ ሥርዓቱ ጤነኛ አይደለም ማለት ይቻላል።ሌላው ሥርዓት መኖሩ የሚታወቀው ገዥና ተገዥ ውዴታና ግዴታቸውን ማወቅ ሲችሉ ነው። በሥርዓት ለመምራት ህዝቡን ሥርዓት ማስተማር ተቀዳሚ ተግባር ሊሆን ይገባዋል። ህዝቡ የማያውቀውን፣ ያልተቀበለውን፣ እምቢ እያለ በኃይል የተጫነበትን ተከፋፍሎ የመኖር ሥርዓት ለማስተካከል ጊዜ ባይወሰድ ከሁሉ የተሻለ መልካም ነው። መንግሥት ይህን ማድረክ ከቻለ ግዴታውን ተወጣ ሊባል ይችላል። 

Tuesday, May 1, 2018

"ክፉውን ስለ ክፉ ፈንታ አትመልሱ"


ስለ ክፋት ታሪካዊ አመጣጥ በመጠኑ ለመጠቆም አሰብኩና ምናልባት የክፋት ሰዎችን ቅር ያሰኝ ይሆን የሚል ሀሳብ ጎበኘኝ ነገር ግን ክፋት ምንጊዜም በጎ አያስብምና ወደ ኋላ ትቶ እውነቱን ማሳየቱ የክፋትን ጎጅነት ብዙ ሳይረዱ የክፋት ሰላባ የሆኑ ወገኖቻችን ማንቃት ይገባልና የግል ሃሳቤን ላካፍል ወደድኩ። 

ሰዎች በባህሪያቸው ክፉ ናቸው ከማለት ይልቅ የአንዳንድ ሰው ባህርይ የክፋት አባት ለሆነው ለዲያብሎስ ምቹ ሆኖ ስለሚገኝ የሰይጣን ፈረስ ሊሆን ይችላል ማለቱ ይቀላል። በቅዱስ መጽሐፍ ከሰውም ከእንስሳም ተንኮለኛ የተባሉ አሉ። ነገር ግን ባህርያቸው ሆኖ ሳይሆን የክፋት አባት ለሆነው ለዲያብሎስ ምቹ ሆነው በመገኘታቸው ነው። ለምሳሌ ይሁዳን ብንወስድ; በፊቱ ካለው በረከት ይልቅ ለማይጠቅም ለሚጠፋ ገንዘብ ልቡን ስለከፈተ፦  "፤ ሰይጣንም ከአሥራ ሁለቱ ቍጥር አንዱ በነበረው የአስቆሮቱ በሚባለው በይሁዳ ገባ፤  (ሉቃ22: 3)" ይላል።  እንዲሁም አስቀድሞ በሰው ልጅ ላይ ዲያብሎስ ሞትን ሲያመጣ በእባብ ተመስሎ እንደሆነ አይዘነጋም። "፤ እባብም እግዚአብሔር አምላክ ከፈጠረው ከምድር አውሬ ሁሉ ይልቅ ተንኰለኛ ነበረ። ዘፍ 3: 1)"