Tuesday, April 24, 2018

የሚሰማ መሪ

ከፍጥረታት ሁሉ አወቂና ክቡር ሆኖ የተፈጠረ እንደ ሰው ያለ ፍጡር አልተገኘም። ይህን ክቡርና አዋቂ የሆነ ፍጡር ለመምራት በእውቀትም  ሆነ በችሎታ ልቆ መገኘት ይጠይቃል። ከስነፍጥረት ጀምሮ ያለውን ታሪክ ስናነብ መሪዎች ነበሩ። ምንም እግዚአብሔር መርጦ መሪ ቢያደርጋቸውም በአስተሳሰባቸው ከሚመሩት ህዝብ በታች ሆነው በመገኘታቸው ፍጻሜያቸው ያላማረ ብዙዎች ናቸው። ብዙ ምሳሌ ማንሳት ይቻል ነበር  ነገር ግን በሰው ሁሉ ዘንድ የታወቀ ስለሆነ ወደ ዋናው ሃሳቤ ልግባ።

የተነሳንበት ርእስ የተለያዩ ትርጉሞች ሊሰጥ የሚችል ቃል ስለሆነ በማጥበቅና በማላላት እንዲሁም በመተርጎም ፍሬ ሃሳቡን ማግኘት እንችላለን። ስናጠብቀው ሁሉ የሚሰማው, ሁሉ እሽ በጄ የሚለው እንዲሁም የሚደመጥ ወ ዘ ተ ማለት ሲሆን ስናላላው ደግሞ የሚሰማ,የሚያዳምጥ, ለሃሳቦች ቦታ የሚሰጥ ወ ዘ ተ ልንለው እንችላለን።

Friday, April 6, 2018

በትንሳኤ ላይ ትንሳኤ

ክርስቶስ አንድ ጊዜ ሞቶ የሰውን ልጆች ነጻ ካወጣ በኋላ በክብር ተነስቷል። በዚህም ምክንያት በእርሱ ያመኑ ክርስቲያኖች የትንሳኤውን እለት በየዓመቱ ያከብሩታል። ሞቱን ስናስብ ሞተን እንደነበር እናስባለን ትንሳኤውን ስናከብር ሞተን እንደማንቀር በክብር እንደምንነሳ እንናገራለን። ስለዚህ በእርሱ ያመኑ ሁሉ ሞቱንና ትንሳኤውን ያስቡ ዘንድ ይገባል።

የክርስቶስን ትንሳኤ ከውድቀት ከመነሳት ጋር ብናከብረው እውነተኛ ትንሳኤ ይሆናል። እኛ ሳንነሳ እሱ ተነሳ ብንል ትርጉሙ አልገባንም ማለት ነው። ከክፋት፣ከተንኮል፣ ከምቀንነት፣ ከዘረንነት ወንበር ላይ ተነስተን የፍቅርና የሰላም ዓርማ የሆነውን መስቀሉን ይዘን የክፋት ሁሉ ባለቤት የሆነውን ሰይጣን ዲያቢሎስን ከእግራችን በታች መጣል ካልቻልን የክርስቶስ ትንሳኤ ተካፋዮች እንዴት ልንሆን እንችላለን? ስለዚህ በየደረጃው ያለን ሁላችን አንዱ ጌታ ስለሁላችን ሞቶ ትንሳኤን እንዳጎናጸፈን ከያለንበት የክፋት ባርነት መንፈስ ተላቀን ለመነሳት የሰላምና የፍቅርን ጋሻ ጦር እንልበስ።

Wednesday, April 4, 2018

ክፉ ምክር

እንበለ ደዌ ወህማም እንበለ ፃማ ወድካም አመ ከመ ዮም ያብጽሃነ ያብጽህክሙ ለብርሃነ ትንሳኤሁ በፍስሃ ወበሰላም አሜን። አይሁድ በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የሞት ፍርድ ለመፍረድ የመጨረሻውን ምክር ያደረጉት ረቡእ እንደ ሆነ በቅዱስ  መጽሐፍ ተጽፏል። ይሁን እንጅ ከዚያም በፊት በተለያዩ ጊዜያት በእርሱ ላይ ምን እንደሚያደርጉ ሲማከሩ ነበር። በህዝቡ ፊት ያደርገው የነበረው መልካም ነገር ምክንያት አሳጥቷቸው እንጅ ሊይዙት ሲፈልጉ ቆይተዋል። 

የአይሁድ ክፉ ምክርና ጥላቻ ከቅንዓት የመጣ እንደሆነ እስከ ሀገረ ገዥው ጲላጦስ ድረስ የታወቀ ነበር።በዚህም ምክንያት ለሞት አሳልፎ ላለመስጠት ብዙ ሞክሯል። ይሁን እንጅ የእነሱን ፈቃድ ለመፈጸም ሲል እያወቀ አሳልፎ ሰጥቷቸዋል። ትልቁ በደል እንኳን ለሞት የሚያበቃ ለክስ የሚሆን መረጃ እንደሌላቸው እያወቀ ሁከት ስላበዙ እራሱን ነጻ ለማድረግ እጁን ታጥቦ ጌታን ግን አሳልፎ ሰጥቷቸዋል። 

Monday, April 2, 2018

'ነጻነት ከመንግስት ለህዝብ የሚበረከት ስጦታ አይደለም' (ዶ/ር አቢይ አህመድ)

ከእግዚአብሔር ለሰው ልጆች ከተሰጡት ጸጋዎች አንዱ የንግግር ስጦታ ሲሆን በተለይ ለመሪዎች አስፈላጊ መሆኑ አይካድም። ብዙ የእግዚአብሔር ሰዎች ለሰውም ለእግዚአብሔርም የሚመች ንግግር ከአንደበታቸው በመውጣቱ የተጣመመውን ማቅናት ችለዋል። በተሰጠን ጸጋ በአግባቡ ከተጠቀምንበት ዋጋ ይገኝበታል። ብዙዎች ግን ይህን ታላቅ ጸጋ ለክፉ ተግባር ሲጠቀሙበት አይተናል። 

ዶ/ር አቢይን በሚዲያ ስንተዋወቃቸው  ቃል ይገድላል ቃል ይተክላል ብለውን ነበር። በዚህም ምክንያት አብዛኛው የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲህ ዓይነት መሪ በሰጠን እያለ ሲመኝ ሰንብቷል። ምኞቱም አልቀረ ቃሉን የተናገሩት መሪ ሆነዋል። በመጀመሪያ የፓርላማ ንግግራቸውም ያንኑ የንግግር ጸጋቸውን ተጠቅመው ተስፋ እርቆት የነበረውን የኢትዮጵያ ህዝብ ተስፋው እንዲለመልም አድርገዋል።