Saturday, March 31, 2018

ፍቱና አምጡልኝ



ወንጌላዊው ማቴዎስ እንደጻፈው ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተመቅደስ ገብቶ በዚያ የሚሸጡትንና የሚለውጡትን ከመገሰጹ በፊት ከደቀመዛሙርቱ ሁለቱን ልኮ በእስራት ላይ ያሉ አህያና ውርንጭላዋን ፈትተው እንዲያመጡ አዞ ነበር። አትፍቱ የሚላችሁ ቢኖር ለጌታ ያስፈልጉታል በሉ የሚል መመሪያም ሰጥቷቸው ነበር። የሰው ልጆችን ሁሉ ከእስራት ሊፈታ እንደመጣ ሲያጠይቅ ይህን ተናገረ። ለምን ትፈታላችሁ የሚላችሁ ቢኖር ለጌታ ያስፈልጉታል በሉ አላቸው።  እነሱም እንደታዘዙት ለጌታ ያስፈልጉታል ብለው ፈትተው አምጥተውለታል።  ቃሉም እንዲህ ይነበባል " ወደ ኢየሩሳሌምም ቀርበው ወደ ደብረ ዘይት ወደ ቤተ ፋጌ ሲደርሱ፥ ያንጊዜ ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ ሁለት ላከ፥እንዲህም አላቸው፦ በፊታችሁ ወዳለችው መንደር ሂዱ፥ በዚያን ጊዜም የታሰረችን አህያ ውርንጫም ከእርስዋ ጋር ታገኛላችሁ፤ ፈትታችሁ አምጡልኝ።ማንም አንዳች ቢላችሁ፦ ለጌታ ያስፈልጉታል በሉ፤ ወዲያውም ይሰዳቸዋል።ለጽዮን ልጅ፦ እነሆ፥ ንጉሥሽ የዋህ ሆኖ በአህያ ላይና በአህያይቱ ግልገል በውርንጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል በሉአት ተብሎ በነቢይ የተነገረው ይፈጸም ዘንድ ይህ ሆነ።ደቀ መዛሙርቱም ሄደው ኢየሱስ እንዳዘዛቸው አደረጉ፥ ማቴ 21፥1"

Friday, March 30, 2018

"ባደርገውም እሞታለሁ ባላደርገውም አልድንም"

ህዝበ እስራኤል በምርኮ ሳሉ በባቢሎን የምትኖር ከእስራኤል ወገነ የሆነች ሶስና የምትባል አንዲት ሴት ነበረች። ይህች ሴት ከልጅነቷ ጀምሮ ህገ እግዚአብሔርን እየተማረች ነበር ያደገችው። እግዚአብሔር ይገድላል እንዲሁም ያድናል የሚለው ጽኑ እምነት የነበራት እና  በምግባሯም እጅግ የተወደደችና የተከበረች ሴት ነበረች። ከዚህም ሌላ እጅግ መልከ መልካምና ማራኪ ውበት ነበራት።  ባሏ ኢዮአቄም የሚባል ከሁሉ የተከበረና ባለ ፀጋ ነበር። በመሆኑም ከአይሁድ ወገን ብዙዎች ለጉዳያቸው ወደ እርሱ ይመጡ ነበር። ከባቢሎን ኃጢአት እንዲጠበቁ ህዝቡን እንመክራለን የሚሉ ሁለት የተሰወረ ተንኮል ያለባቸው ሁለት የአይሁድ መምህራን ነበሩ። እነዚህ ክፉ መምህራን ለኢዮአቄም ባለሟል ነበሩና ሶስናን እለት እለት እየተመለከቱ በዝሙት ፍቅር ወደቁ። አንዱ ለሌላው በልቡ ያለውን ሳይነግር አሳቻ ቦታ እየፈለጉ ሳለ ከቤቷ አቅራቢያ በሚገኘው የአትክልት ስፍራ እንደ ሥርዓቱ ለመታጠብ በሄደች ጊዜ ከሷ ቀድመው ወደ አትክልቱ ስፍራ በመግባት ተሰውረው ስለነበር አገልጋዮቿን አሰናብታ ለመታጠብ ስትዘጋጅ ከተደበቁበት ወጥተው በዝሙት እንድረስብሽ አሏት። ህገ እግዚአብሔርን ጠንቅቃ የምታውቅ በመሆኗ ይህን ኃጢአት እንደማትፈጽም ነገረቻቸው። እነሱ ግን በዝሙት አይናቸው ታውሮ ይህን ካልፈጸመች ያለበደሏ በሀሰት አስመስክረው እንደሚያስገድሏት ነገሯት። እሷም እኒያ አስመሳይ መምህራን ይህን ክፉ ኃጢአት እንድትፈጽም ባስጨነቋት ጊዜ እንዲህ አለች "ባደርገውም እሞታለሁ ባላደርገውም አልድንም" ይህን ብላ ድምጿን አሰምታ ጮኽች በዚያ የነበሩ ሰዎች ሲሰበሰቡ እነዚያ ተንኮለኞች መምህራን አስቀድመው እንደተናገሩት የሀሰት ቃል መናገር ጀመሩ ህዝቡም የመምህራኑን ቃል በመስማት በድንጋይ ተወግራ መገደል አለባት በማለት ተስማሙ። ሊገድሏት ሲሄዱ ያመነችው አምላክ ህፃን ልጅ ልኮ የነዚያን ተንኮለኞች መምህራን ስውር ሴራ ገልጦ በማውጣት የሷን ሞት እነሱ እንዲሞቱ አድርጓል። ያ ሶስናን ከሞት የታደገ ወጣት ነቢዩ ዳንኤል ነበር።  መ. ሶስና ቁ 5

Tuesday, March 20, 2018

እናንተን የጣለ እኔን ይጥላል ሉቃ 10፥16

በኛ ዘንድ የተዋረደውን ሳይሆን ያልተዋረደው ምንድነው ብሎ መጠየቅ ሳይሻል አይቀርም። ኢትዮጵያዊነት ከተኮነነ ሰነባበተ። ለኢትዮጵያ ትልቅ ውለታ ያበረከተችው ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ከተናቀች ውሎ አደረ። መቼም ይህን እውነት አለመናገር በሰውም በእግዚአብሔርም ዘንድ ያስጠይቃል። የትኛው በደል ይሆን ይህን ሁሉ ነገር በአንድ ወቅት ያመጣብን? ሰው ይበድላል። እግዚአብሔር ሊያስተምር እንደሚቀጣም እናምናለን እኛ ግን እየተማርን አይደለም። ሊያስተምረን ያመጣውን መከራ ለጥፋት እያደረግነው ይመስላል።  ኢትዮጵያ የሚለውን ስም መጥራት የማይፈልግ ትውልድ ምድራችን አብቅላ አየን። ሁሉን እንደራሷ ልጆች አድርጋ ፊደል አስቆጥራ፣ መጠለያ ሰጥታ፣ በጎ ምግባር አስተምራ ሀገርን ከነሙሉ ታሪኩ ለዛሬው ትውልድ ያስረከበች ቤተክርስቲያን አንደበታቸው የስድብ አፍ በተመላ ክፉ ትውልዶች ተሰደበች ይህ ያመጣው መርገም ለብዙዎች ተርፎ ሰላም ከራቀን ሰነባበተ።