Wednesday, February 26, 2014

መጠራታችሁን ተመልከቱ


እግዚአብሔር ፍጥረታትን ሲፈጥር ያለ ዓላማ የፈጠረው ፍጥረት እንደ ሌለ መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል። የፍጥረት ዓይነቱ ልዩ ልዩ እንደሆነው ሁሉ የተፈጠረለት ዓላማውም ልዩ ልዩ ነው። በተለይ የሰው ልጅ ከፍጥረታት ሁሉ ይለያል። ፍጥረታት በሙሉ የራሳቸውን መልክ ይዘው ሲፈጠሩ ሰው ግን እግዚአብሔርን መስሎ ነው የተፈጠረው። ይህም በመሆኑ ዘላለማዊነትና ገዥነት ተሰጥተውት ነበር። በዚህ ክብርና ልዕልና ጸንቶ የቆየው ግን ለሰባት ዓመታት ብቻ ነበር። በጥንተ ጠላቱ ዲያቢሎስ ተታሎ ከአስተዳዳሪነት ወደ ባርነት ከዘላለማዊነት ወደ ኃላፊነት ከገነት ወደ ምድረ ፋይድ ከተሸጋገረ በኋላ ይገዛቸው ያስተዳድራቸው ዘንድ ሙሉ ስልጣን ሰጥቶት የነበረው እንስሳት እንኳን ሸሹት። ለፈጣሪው ያልታመነ ለኛ የሚራራ ልብ እንዴት ይኖረዋል ያሉ ይመስላል። 

Monday, February 24, 2014

በሁሉ አመስግኑ

በአንድ ወቅት አንድ መልካም ሰው ወንጀል ሰርተሃል ተብሎ ፍርድ ቤት ቀረበ አሉ፤ ታዲያ ይህ ሰው ወንጀሉን የፈጸመው ሆን ብሎ ሳይሆን።በአጋጣሚ ነበር፥ ፍርድ ቤት ቀርቦ ዳኛው የምስክሮች ቃል ከሰሙና የቀረበላቸውን ማስረጃ ከመረመሩ በኋላ በሞት እንዲቀጣ ወሰኑበት። በዚህ ጊዜ በፊቱ ላይ ምንም የመረበሽ ስሜት አልታየበትም ነበር። በሁኔታው የተገረሙት ዳኛውና በዙሪያው ያሉት ሰዎች የመጨረሻ የመሰናበቻ ቃሉን ይጠብቁ ጀመር። እግዚአብሔር ይስጥልኝ ክቡር ዳኛ፣ እድሜ ይስጥልኝ፣ ፍርድ የሚሰጥ ዳኛ አያሳጣን ወ ዘ ተ እያለ ምስጋናውን ያወርደው ጀመር  አግራሞታቸው የጨመረው ዳኛ ግራ ተጋብተው ,, የፍርዱን ውሳኔ የተረዳው አይመስለኝም በሞት እንዲቀጣ ነው የተወሰነበት ምናልባት ውሳኔውን በደንብ ካልሰማ አስረዱት,,  አሉ ። ሰውየውም መለሰ ,, ውሳኔውን በደንብ ተረድቻለሁ ፍርዱም ገብቶኛል የመረዳትም ችግር የለብኝም,, ብሎ መለሰ፤ የዳኛው ጥያቄ ቀጠለ ,, ታዲያ እንዴት ነው የሞት ፍርድ እየተፈረደብህ ፍርድ ቤቱን የምታመሰግነው? አሉ ። ,, ጌታየ ከዚህም የከፋ ፍርድ እኮ አለ መቶ ጅራፍ ተገርፎ ይሙት ቢሉስ ይችሉ አልነበር?  ብሎ መለሰ ይባላል።

Friday, February 14, 2014

እስከ መቼ?

ለሰው ልጆች ከእግዚአብሔር ከተሰጡት ስጦታዎች ትልቁ ሃይማኖት ነው። ሰው ከፍጥረታት ሁሉ የላቀ ክብር እንዳለውም የታወቀው በሃይማኖት ኖሮ ከፈጣሪው ጋር ስለሚገናኝ ነው። ታዲያ ይህን ትልቅ ጸጋ አክብሮና ጠብቆ የመኖር ኃላፊነት አለበት። ቅዱሳን እራሳቸውን ለእግዚአብሔር በማስገዛታቸው በዚህ መንገድ ተጉዘው ወደ ዘለዓለም እረፍት እንዲገቡ እግዚአብሔር ሃይማኖትን ሰጥቷቸዋል። ለዚህም ነው ሐዋርያው ቅዱስ ይሁዳ <<  ወዳጆች ሆይ፥ ስለምንካፈለው ስለ መዳናችን ልጽፍላችሁ እጅግ ተግቼ ሳለሁ፥ ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ስለ ተሰጠ ሃይማኖት እንድትጋደሉ እየመከርኋችሁ እጽፍላችሁ ዘንድ ግድ ሆነብኝ ይሁዳ 1፥3 >>  ያለው። የሰው ልጆች  በጸጋ የእግዚአብሔር  ልጅነትን ስላገኙ በሃይማኖት ኖረው ያባታቸውን  የእግዚአብሔርን ርስት እንዲወርሱ የእግዚአብሔር ፈቃዱ ነው።
 
ሃገራችን ኢትዮጵያ የቅዱሳን ሃገር በመሆኗ ህዝቦቿም በአምልኮተ እግዚአብሔር ለብዙ ዘመናት ጸንተው የኖሩ በመሆናቸው ብዙ ቅዱሳን በመንፈስ ቅዱስ ተመርተው ወደ ሃገራችን እየፈለሱ እንደመጡ በብዙ ቅዱሳት መጻሕፍት ላይ ተጽፎ እናገኛለን። ዛሬም ቢሆን በዓለም የሚገኙ የታሪክ ተመራማሪዎች ኢትዮጵያ የሰው ዘር መጘኛ፣ የታሪክ ማህደር መሆኗን እየመሰከሩ ነው። ድንቅ ሃይማኖታዊ ስርዓቷንና ትውፊቷን ለማድነቅ በየእለቱ ብዙ የዓለም ህዝቦች እየጎረፉ ነው።  በኢትዮጵያውያን በኩል የሚታየው ግን  ብዙ ደስ የሚል አይደለም። በተለያየ አቅጣጫ ህዝቡ እየተፈተነ  ነው።  በጎ ምግባርንና ሃይማኖትን የተማረው ከሃይማኖት አባቶቹ ነበር ። ዛሬ ላይ በአባቶቹ ተስፋ በመቁረጥ እምነቱ እየተሸረሸረ በመምጣቱ አህዛቡንም ሆነ መናፍቃኑን መቋቋም አቅቶት በእነሱ እየተማረከ የክፉ ስራቸው ተባባሪ በመሆን ቤተክርስቲያኑንና ሃገሩን ታሪክ አልባ እያደረጋት ነው። 

Thursday, February 13, 2014

ከጽኑ ቍጣውም ይመለስ እንደ ሆነ ማን ያውቃል?

በተለያዩ ዘመናት እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ያለውን ይቅርታ፣ ቸርነትና ምህረት በቅዱሳኑ በኩል ገልጿል። ከዚህም አንዱ ለሰብአ ነነዌ ያደረገላቸው ምህረትና ይቅርታ ሲነገር ይኖራል። በትንቢተ ዮናስ ተጽፎ እንደምናገኘው የነዚህ ህዝቦች ኃጢዓትና በደል በእግዚአብሔር ፊት ደርሶ ነበር ,,  የእግዚአብሔርም ቃል ወደ አማቴ ልጅ ወደ ዮናስ እንዲህ ሲል መጣ።ተነሥተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፥ ክፉታቸውም ወደ ፊቴ ወጥቶአልና በእርስዋ ላይ ስበክ ,, ት ዮና 1፥1 ,, በዚህም የተነሳ ነቢዩ ዮናስን ወደ እነርሱ ልኮት ነበር። ነገር ግን ነቢዩ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ከመፈጸም ይልቅ በራሱ ሃሳብ ተሸንፎ ከእግዚአብሔር ፊት ለመሸሽ ሞከረ። ብዙውን ጊዜ በራሳችን እውቀትና ጥበብ ከእግዚአብሔር ለመሸሽ የምናደርገው ሙከራ ሰው ምን ያህል በራሱ ሞኝ እንደሆነ የሚገለጥበት ነው። የሚገርመው በእውቀትና በጥበብ የተሻሉ ሆነው በሰው ዘንድ የሚታዩ በእግዚአብሔር ተመርጠው ለህዝቡ እረኛ የሆኑ ሰዎች ከእግዚአብሔር ፊት ለመሸሽ ሲሞክሩ እጅግ ይደንቃል። ዮናስም እንዲሁ ነበር ያደረገው። እግዚአብሔር ደግሞ ከተናገረ ያደርገዋል፣ ከጀመረም ይፈጽማል። ዮናስ በራሱ ጥበብ ከእሱ ለማምለጥ ቢሞክርም በጥበበ እግዚአብሔር ከጥልቁ ባህር እና ከአሳ አንበሪ ሆድ በሰላም እንዲወጣ አድርጎት ለነነዌ ሰዎች የእግዚአብሔርን የንስሃ ጥሪ አድርሶላቸዋል።