Friday, November 7, 2025

ክፉውን በመልካም አሸንፍ እንጂ በክፉ አትሸነፍ ሮሜ 12፥1

ከአባቶቻችን የወረስነው አባባል ''የወደቀ ዛፍ ምሳር ይበዛበታል'' ይላል። እውነትም ወድቆ የተገኘ ነገር ሁሉ የፈቀደውን ያደርግበታል ስለዚህ ለማንም የሚጠቅመው ወድቆ አለመገኘት ነው። 

ክፉ የሚባለው ጨካኝ፣ የማይራራ፣ እራስ ወዳድ ሃዘኔታ የሌለው ወዘተ ማለት ሲሆን መልካም ማለት ደግሞ ማዘን፣መራራት፣ ለሌላው ማሰብ፣ በኔ ሊደረግ የማይገባውን በሌላው አላደርግም ወዘተ ብሎ እራስን መግዛት ማለት ነው። አሸናፊነት ሁልጊዜ የበላይ መሆን ወይም ከሌላው በልጦ መገኘት ብቻ አይደለም። ክፉ ለሚያደርግ መልካም መመለስ አሸናፊነት ነው። የበደለን ይቅር ማለት አሸናፊነት ነው። የተቀሙትን መተው አሸናፊነት ነው ከዚህ አንጻር ብዙ ማለት ይቻላል። 

ሰው መሸነፍ የሚጀምረው ተስፋ መቁረጥ ውስጥ የገባ እለት ነው። በተለይ ክርስቲያን በፍሱም ተስፋ መቁረጥ የለበትም። ቅዱስ ጳውሎስ ለእብራውያን በጻፈው መልእክቱ'' እንግዲህ እነዚህን የሚያህሉ ምስክሮች እንደ ደመና በዙሪያችን ካሉልን፥ እኛ ደግሞ ሸክምን ሁሉ ቶሎም የሚከበንን ኃጢአት አስወግደን፥ የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን፥ በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ፤ እርሱ ነውርን ንቆ በፊቱም ስላለው ደስታ በመስቀል ታግሦ በእግዚአብሔር ዙፋን ቀኝ ተቀምጦአልና። በነፍሳችሁ ዝላችሁ እንዳትደክሙ፥ ከኃጢአተኞች በደረሰበት እንዲህ ባለ መቃወም የጸናውን አስቡ'' እብ 12፥1 ብሎ እንደተናገረው ፈተና በማንኛውም መልኩ ቢገጥመን ልናሸንፈው እንደምንችል ከአባቶቻችን ተምረናል።

ክርስትና ከጌታችን ከአምላካችንና ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጀምሮ የደም ዋጋ እየተከፈለበት ዛሬ ላይ የደረሰ ሃይማኖት ነው። ዛሬ በሰዎች ኃጢአት መብዛት የሃሳብ መለያየት በዝቶ ሁሉም የግል ሃሳቡን እያፈለቀ ብዙ ቤተ እምነት (Denomination) ቢፈጠርም መነሻው ግን አንድ ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለኤፌሶን ክርስቲያኖች በጻፈው መልእክቱ  ''በመጠራታችሁ በአንድ ተስፋ እንደ ተጠራችሁ አንድ አካልና አንድ መንፈስ አለ፤አንድ ጌታ አንድ ሃይማኖት አንዲት ጥምቀት፤ከሁሉ በላይ የሚሆን በሁሉም የሚሠራ በሁሉም የሚኖር አንድ አምላክ የሁሉም አባት አለ'' ኤፌ 4፥5  ብሎ እንደተናገረው የዓለማት ፈጣሪ እግዚአብሔር አንድ ነው። ወደ እርሱም የምንቀርብባት መንገድ አንዲት ናት እርስዋም አባቶቻችን የተጓዙባት ለነፍሳቸውም እረፍት ያገኙባት ናት። እርስዋ ቀዳማዊት ናት ደኃራዊት አይደለችም አዳም፣ አቤል፣ሴት፣ሄኖክ፣ኖህ፣አብርሃም፣ይስሃቅ፣ ያዕቆብ፣ ሙሴ፣ዳዊት፣ነቢያት፣ሐዋርያት የተጓዙባት ቀጥተኛ መንገድ ናት። ''ግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ በመንገድ ላይ ቁሙ ተመልከቱም፥ የቀደመችውንም መንገድ ጠይቁ፤ መልካሚቱ መንገድ ወዴት እንደ ሆነች እወቁ፥ በእርስዋም ላይ ሂዱ፥ ለነፍሳችሁም ዕረፍት ታገኛላችሁ፤ እነርሱ ግን፦ አንሄድባትም አሉ'' ኤር 6፥16


ዛሬም እኛ ልጆቻቸው ከአባቶቻችን የወረስናትን መንገድ ትተን በጊዜያዊ ጥቅም ተደልለን ከእውነት ፈቀቅ ልንል አይገባም። ከዚህች መንገድ መውጣት ትልቁ ሽንፈት ነው። ከሰዎች የሚመጣብን ፈተና ሁሉ በእግዚአብሔር ዘንድ ዋጋ የሚያስገንል በመሆኑ ደስ ሊለን ነው የሚገባው። ሲሰድቡን፣ ሲያሳድዱን፣ ሲገድሉን በሥሙ ስለሆነ አሸናፊዎች እኛ ነን። ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳስተማረን '' ሲነቅፉአችሁና ሲያሳድዱአችሁ በእኔም ምክንያት ክፉውን ሁሉ በውሸት ሲናገሩባችሁ ብፁዓን ናችሁ።ዋጋችሁ በሰማያት ታላቅ ነውና ደስ ይበላችሁ፥ ሐሴትም አድርጉ፤ ከእናንተ በፊት የነበሩትን ነቢያትን እንዲሁ አሳድደዋቸዋልና'' ማቴ 5፥11

Friday, October 31, 2025

እረኞች ሆይ፥ የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ ሕዝ 34፥7

ቅዱሱ መጽሐፋችን መጽሐፍ ቅዱስ ወንድም ወንድሙን መግደል የጀመረበትን ምክንያት በግልጽ ይነግረናል ዘፍ 4፥8 ነገር ግን ምክንያቱን ለመቀበል ከአእምሮ በላይ በመሆኑ እጅግ ያስደንቃል። እንኳን ሰው ይቅርና እንስሳ የራሱን ወገን በበጎ የሚያይበት ተፈጥሯዊ ስጦታ ታድሏል፦ ነገር ግን የሰው ልጅ ከእንስሳት አንሶ ሰው ሰውን እየበላ የክፋት እርሃቡን ለማስታገስ ሲሮጥ ማየት እጅግ ያሳዝናል። ሰላማውያን የምንባለውም እኛ ከመደጋገሙ የተነሳ እየለመድነው በመምጣታችን እንደቁም ነገር ለመቁጠር እየተቸገርን እንደሆነ በግልጽ እየታየ ነው።  ሰሞኑን በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ አርሲ ዞን በተለያዩ ወረዳዎች ሥር የሚገኙ በርካታ ምዕመናን በጽንፈኞች እንደተገደሉ ሰምተናል። ይሁን እንጅ ከመንግሥትም ሆነ ከቤተክህነት ለሟቾችም ሆነ ለቤተሰቦች እንደዜጋ እና እንደ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ምዕመን ክብር እንዳልተሰጣቸው በተላለፉት መልእክቶች መረዳት ይቻላል። የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ምዕመን መገደሉ በዚህ ደረጃ መቅለሉ በጣም ያሳዝናል።



የንፁሐን ደም የሚያመጣውን ወይም ያመጣውን መዘዝ ማወቅና መረዳት ለመንግሥትና ለሃይማኖት መሪዎች እንዴት ተሳናቸው?  እንዲሁም ይህን በየጊዜው የሚፈስ ደምና እንባ የምንመለከት ወገኖች እንዴት በጋራ መጮህ አቃተን? ብለው የሚጠይቁ ብዙዎች ናቸው። ህጻናት፣ እናቶች፣ አባቶች፣ ዲያቆናት፣ ካህናት፣መነኮሳት (እስከ አሁን ጳጳሳትን አይጨምርም ለወደፊቱ ግን ስጋት አለን) ናቸው ደማቸው እየፈሰሰ ያለው። ማነው የንጹሐንን ደም ከመፍሰስ መታደግ ያለበት? የመንግስትም ሆነ የሃይማኖት መሪዎች ዘመኑን የዋጀ የአመራር ሥርዓት መዘርጋት ካልቻላችሁ ኃላፊነታችሁን እየተወጣችሁ አይደለም። ህዝብ መሪ አለኝ ብሎ ከልፋቱ ጥሪቱን ግብር እየከፈለ የሚኖረው ሰላምና ደህንቱን የሚያስጠብቅለት አካል አለኝ ብሎ አምኖ ነው።

Saturday, October 18, 2025

የሃይማኖት ሰው ምግባር


1, ከእግዚአብሔር ሌላ አምላክ የለውም

2, የፈጣሪውን ስም በከንቱ አያነሳም

3, እለተ ሰንበትን ያከብራል


Saturday, October 11, 2025

ድንግል ማርያምን ማየት የተሳነው ኢየሱስ ክርስቶስን እንዴት ማየት ይችላል?

 ከመንበሩ ላይ ተቀምጦ የምናየው ስእል ምስለ ፍቁር ወልዳ ብለን የምንጠራም የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ልጇን ኢየሱስ ክርስቶስን ታቅፋ የሚያሳይ ስእለ አድህኖ ነው ብየ ልጽፍ አሰብኩና ይህን የማያውቅ ሰው ሊኖር አይችልም የሚል ሃሳብ ውስጤን ስለሞገተው በቀጥታ ማስተላለፍ ወደፈለኩት ሃሳብ ገባሁ። ሰሞኑን ስለ ቅዱሳን ስእላት የተነሳውን የተዛባ ሃሳብ ባሰብኩ ጊዜ ይህን ጻፍኩ።



Thursday, October 2, 2025


 በዚያች ሰዓት ደቀ መዛሙርቱ ወደ ኢየሱስ ቀርበው፦ በመንግሥተ ሰማያት ከሁሉ የሚበልጥ ማን ይሆን? አሉት። ሕፃንም ጠርቶ በመካከላቸው አቆመ እንዲህም አለ፦ እውነት እላችኋለሁ፥ ካልተመለሳችሁ እንደ ሕፃናትም ካልሆናችሁ፥ ወደ መንግሥተ ሰማያት ከቶ አትገቡም። እንግዲህ እንደዚህ ሕፃን ራሱን የሚያዋርድ ሁሉ፥ በመንግሥተ ሰማያት የሚበልጥ እርሱ ነው። እንደዚህም ያለውን አንድ ሕፃን በስሜ የሚቀበል ሁሉ እኔን ይቀበላል፤ በእኔም ከሚያምኑ ከነዚህ ከታናናሾቹ አንዱን የሚያሰናክል ሁሉ፥ የወፍጮ ድንጋይ በአንገቱ ታስሮ ወደ ጥልቅ ባሕር መስጠም ይሻለው ነበር። ማቴ 18፥1