Monday, December 29, 2025
ጾመ ጋድ (ገሃድ)
Friday, December 19, 2025
የእግዚአብሔርን ዝማሬ በባዕድ ምድር እንዴት እንዘምራለን?'' መዝ 137፥1
ሕዝበ እሥራኤል የፈጣሪያቸውን ህግና ሥርዓት መጠበቅ እየተሳናቸው ብዙ ጊዜ በስደትና በጦርነት ተቀጥተዋል። ይሁን እንጅ እግዚአብሔር አምላክ አስቀድሞ ለአባቶቻቸው የገባው ቃል ኪዳን ስላለ የጠፉ ቢመስሉም እንደገና ያበረታቸዋል።
ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ የአባቶቹን ሃዘንና ሰቆቃ በምርኮ ሳሉ የደረሰባቸውንና ያደረጉትን አስታውሶ የተናገረውን ነው መነሻ ያደረኩት ''በባቢሎን ወንዞች አጠገብ በዚያ ተቀመጥን፤ ጽዮንንም ባሰብናት ጊዜ አለቀስን።በአኻያ ዛፎችዋ ላይ መሰንቆቻችንን ሰቀልን። የማረኩን በዚያ የዝማሬን ቃል ፈለጉብን፥ የወሰዱንም፦ የጽዮንን ዝማሬ ዘምሩልን አሉን። የእግዚአብሔርን ዝማሬ በባዕድ ምድር እንዴት እንዘምራለን?'' መዝ 137፥1
ሀገራችን ኢትዮጵያ በገጠማት ችግር ምክንያት ልጆቿ ስደትን እንደ ትልቅ እድል በመቁጠር በሰው ሀገር መኖርን ተለማምደዋል። ብዙዎች በገዛ ሀገራቸው የስደተኛነት ስሜት እየተሰማቸው የሰው ሀገር ይናፍቃሉ። ከዋና ከተማዋ አዲስ አበባ በመኪና ተጉዞ ቤተሰብ ማግኘት የማይታሰብ እየሆነ ነው። አዲስ አበባ ተውባለች ደምቃለች የሀገሪቱ ሰፊው ገጠራማ ክፍል ግን በሰላም እጦት ጭንቀት ላይ ይገኛል። ጦርነት፣ ርኃብ፣ ስደት ለእኛ ለኢትዮጵያውያን እንደ አዲስ ነገር የሚነገር ዜና አይደለም። በዚህም ምክንያት አንድ ሰው ተበደልኩ ብሎ ሲናገር ወይም አንዱ ስለሌላው መበደል ሃሳብ ቢሰጥ እንደቁም ነገር መቁጠር ካቆምን ሰነባብተናል። ይህ ሁሉ ችግር እያለ በዚህ ሰቆቃ ለበዛበት ማህበረሰብ የማይሆኑ አጀንዳዎችን የሚፈጥሩ አንዳንድ የቤተክርስቲያን አገልጋዮች በውዳሴ ከንቱ ተጠልፈው ''በቁስሉ ላይ እሾህ ስደድበት'' በሚመስል መልኩ ህዝቡን ግራ ያጋቡታል። ቢቻል ስለሃገር ሰላምና አንድነት መሥራት ይገባ ነበር ካልሆነም ህዝቡ ካለበት ችግር የሚወጣበትን ምክርና በጎ ሃሳብ ማቅረብ ሲገባ መለያየትን የሚያመጣ የግል ሃሳብ ማምጣት ለህዝብ ዴንታ ቢስ መሆን አይደለምን?
እውነት ለእኛ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ልጆች በዚህ ሰዓት ጸሎት ነው መዝሙር ነው የሚያስፈልገው? ስሜትን ተወት አድርጎ በማስተዋል ነገሮችን ብናደርግ እግዚአብሔርም ይሰማናልና ቆም ብለን እናስብ።
መዝሙር ማለት ለእግዚአብሔር የሚቀርብ የደስታ ጸሎት ወይም ምስጋና ማለት ነው ''ደስ የሚለውም ማንም ቢኖር እርሱ ይዘምር'' ያዕ 5፥13 እውነት እኛ ኢትዮጳያውያን በዚህ ወቅት ደስተኞች ነን?
