Saturday, August 5, 2023

''ረኃብ ምንድነው?''

አባቶቻችን እንደነገሩን ረኃብ ምንድነው? ብሎ የጠየቀው የእስራኤል ንጉሥ የነበረው የቅዱስ ዳዊት ልጅ ንጉሥ ሰሎሞን ነው። ንጉሥ ሰሎሞን በእግዚአብሔርም በሰውም የተወደደና ከፈጣሪው ልዩ ጥበብና ሞገስ የተቸረው አስተዋይ ንጉሥ እንደነበር በቅዱስ መጽሐፍ ታሪኩ በሰፊው ተመዝግቧል በመሆኑም ከውልደቱ እስከንግሥናው ድረስ በቤተመንግስት በእንክብካቤና በተቀማጠለ ህይዎት የኖረ ሰው ነው  ከእለታት አንድ ቀን በቤተመንግስቱ በክብሩ ዙፋን ላይ ተቀምጦ ሳለ የተቸገረ፣ የተራበ፣ የተጠማ ሰው ወደ ደጁ መጣና እራበኝ እርዱኝ ብሎ ጮኸ ነገር ግን ወታደሮቹ እየደበደቡና እየገፉ ከአካባቢው ሲወስዱት በማየቱ ተደንቆ ምክንያቱን ጠየቀ የወታደሮቹም እራበኝ እርዱኝ እያለ ነው በአንተ ግዛት ሥር እንዴት የተራበ ሊኖር ይችላል? ብለው መለሱለት በዚህን ጊዜ ነበር ከላይ በርዕሳችን ላይ ያነሳነውን ጥያቄ ንጉሥ ሰሎሞን የጠየቀው ''ረኃብ ምንድነው?''(ታሪኩ ሰፊ ስለሆነ በሌላ ጊዜ እንመለስበታለን) በእውነት ረኃብ ምንድነው? ስንቶቻችን ነን ረኃብን ተርበን ያወቅነው? ስንቶቻችን ነን መጠማትን ተጠምተን ያወቅነው? ስንቶቻችን ነን መገፋትን ተገፍተን ያወቅነው? ስንቶቻችንስ ነን የትላንቱን መራብና መጠማት እንዲሁም መገፋት ያልዘነጋነው? ስንቶቻችን ነን የሌሎችን እንባ አይተን ያለቀስነው? የሰው ትንሹ ቸርነት በተፈጥሮ ያገኘው ሲያዝኑ አይቶ ማዘን ሲደሰቱ አይቶ መደሰት ነበር ቢያንስ ይህን ማድረግ ቢያቅተን እንዴት ሰዎች ተርበው እራበኝ፣ ተጠምተው ጠማኝ፣ መኖር ተነፍገው በህግ አምላክ ልኑር ሲሉ አፋችሁን ዝጉ እንላለለን?

ሰው ከእንስሳ የሚለየው የሚያገናዝብ ፍጥረት በመሆኑ ነው። መገንዘብ ማለት ደግሞ የክፉውንና የመልካሙን፣ የቀኝና የግራውን፣ የኋላና የፊቱን ወ ዘ ተ ለይቶ ማወቅና መረዳት ማለት ነው። ሰው ይህን ፀጋውን በተለያዩ ምክንያቶች ሊያጣ ይችላል። በጤና መታወክ፣ ከአቅም በላይ በሆነ ጫና ምክንያት፣ በራስ ወዳድነት፣ በንዝህላልነት፣ በእውቀት ማነስ፣ በምቾት ብዛት፣ በጥላቻ መታወር ወ ዘ ተ ብለን መዘርዘር እንችላለን።