Friday, August 17, 2018

"ላለፈ ክረምት ቤት አይሰራም"

ዛሬ ላይ ብዙዎች ኢትዮጵያን የመሰለች እናት እያላቸው ማንነት ፍለጋ የሚዋትቱት  በገዛ ሀገራቸው እንደ ባይተዋር በመታየታቸው እንደሆነ ግልጽ ነው። "ላለፈ ክረምት ቤት አይሰራም" እንዲሉ ስላለፈው መጥፎ ነገር ጊዜ ማጥፋት ሞኝነት ነው። መፍትሄው። ያለፈውን በታሪክነቱ መማሪያ አድርጎ ለወደፊቱ  ይህን ክፉ ተግባር የሚፈጽሙ ወገኖችን እድል በመንሳት ታግሎ እኩልነት ማምጣት ብቻ ነው ። አባቶቻችን "በሀገርና በእናት ቀልድ የለም" ይላሉ ታዲያ እግዚአብሔር የኢትዮጵያ ልጆች አድርጎን በሰዎች ምክንያት እንዴት በእናታችን እንደራደራለን?

በግልጽ መታወቅ ያለበት የግል ማንነትና የጋራ ማንነት የተለያዩ ናቸው። በኢትዮጵያ ምድር ለተገኘን ሁላችን ወደድንም ጠላንም ኢትዮጵያዊነት ማንነታችን ነው። ይኽን ማንነት ደግሞ ሰዎች የሰጡን ማንነት ሳይሆን ከእግዚአብሔር ያገኘነው ነው። ይኽን ማንነት በተልካሻ ምክንያት የሚጥል የተሸናፊዎች ሁሉ ተሸናፊ ነው። እናት አንድ ጊዜ ትወልዳለች ለሁልጊዜ እናት ትባላለች። የወለደች እናት እያለች በምንም መስፈርት ሌላዋ እናት ልትባል አትችልም።

ስለዚህ እኛ ዛሬ ከእናታችን ጉያ ለመውጣት የምንፈራገጥ ሁላችን ነገ ምንደኛ ሆነን ለመኖር እየታገልን እንደሆነ እናስብ። እኔ በግሌ ሁልጊዜ ጸሎቴ ኢትዮጵያዊ የሆነ ሁሉ ወንድሜም እህቴም እንደሆነ የማስብበት ህሊና ፈጣሪ አምላክ እግዚአብሔር  እንዳይነሳኝ ነው። ለሁላችንም አስተዋይ ልቦና ያድለን።

Tuesday, August 14, 2018

እኛና እነሱ እየተባባልን እንዴት እንደመር?

አባቶቻችን ስለ ነገሩን ብቻ ሳይሆን ሀገር በተግባሯ እናትን ትመስላለች። የተፈጥሮን ህግ ጥለን እንደ እንስሳት እንሁን ካላልን በቀር የአንድ እናት ልጆች ወንድማማቾች፣ እህትማማች ይባላሉ። ይህን መቀበል የማይፈልግ ትውልድ የአንድ እናት ልጅ ወይም የአንድ ሀገር ህዝብ ሊባል ከቶ እንዴት ይችላል? ብዙ ጊዜ በጎውን ደጋግመን እያወራን ክፉው ነገር አስተዋይ በማጣቱ ከአቅም በላይ እያደገ የመጣ ይመስላል። ጤናማ ያልሆኑ ሃሳቦችን እውነት ነው እያልን ስንቀበል በመኖራችን ዛሬ ላይ ያለነው ትውልዶች የራሳችንን ስንፍና ወደ ጎን በመተው፤ ህይዎታቸውን ያለ ስስት ለሀገራቸው በመስጠት ሀገር ያስረከቡንን አባቶቻችንን ሽቅብ የምንራገም ተስፋ አልባ፣ ወደ ኋላ እንጅ ወደፊት ማየት የማንችል ትውልዶች ሆነናል። Where is Ethiopia?

Monday, August 6, 2018

ፈጥኖ ደራሽ መንግሥት እንዲኖረን እመኛለሁ

ይህን ጽሁፍ ስጽፍ የዶ/ር አቢይን ጥረትና ድካም ከንቱ በማድረግ እንዳልሆነ እንዲታወቅልኝ አደራ እላለሁ። በሱማሌ ክልል የደረሰውን አሰቃቂና ዘግናኝ ድርጊት በማየትና በመስማት ይህን ጻፍኩ።  በሀገራችን ለምን ተመሳሳይ ስህተቶች እንደሚሰሩ እስከ አሁን በግሌ የተረዳሁት ነገር የለም። የትላንቱን እየኮነንን ለምን ዛሬ ከትላንቱ የባሰ ጥፋት እንዲጠፋ እድል እንደምንሰጥም አልገባኝም። በኢትዮጵያ ምድር የሰው ህይዎት ክቡር መሆኑ ታምኖ ጥበቃ ሲደረግለት ማየት በጣም ነው የናፈቀኝ።